የታይሮኢድ ሆርሞን መብዛት ( ሃይፐርታይሮይዲዝም)

Biruh Tesfaye
Dec 18, 2025
undefined

ታይሮይድ በሰውነትዎ አንገት ፊት ለፊት የሚገኝ ትንሽ፣ የቢራቢሮ ቅርጽ ያለው እጢ ነው።  ይህ እጢ ታይሮክሲን (T4) እና ትራይአዮዶታይሮኒን (T3) የሚባሉ ሁለት ዋና ሆርሞኖችን ያመርታል። እነዚህም ሆርሞኖች ሰውነት ኃይል የሚጠቀምበትን መንገድ የሚቆጣጠሩ ሆርሞኖች ናቸው። በሰውነትዎ ውስጥ ያሉትን በሁሉም የአካል ክፍሎች ላይ ተጽእኖ ስላላቸው የሰውነትዎ በጣም አስፈላጊ ተግባራትን ይቆጣጠራሉ። ለምሳሌ፣ በአተነፋፈስዎ፣ በልብ ምትዎ፣ በክብደትዎ፣ በምግብ መፈጨትዎ እና በስሜትዎ ላይ ተጽዕኖ ያሳድራሉ።

ሃይፐርታይሮይዲዝም የታይሮይድ እጢ ሰውነትዎ ከሚያስፈልገው መጠን በላይ የታይሮይድ ሆርሞን ሲያመነጭ እና ሲልቅ የሚከሰት ሲሆን፣ ይህም የሰውነትን ሜታቦሊዝም (የሰውነት ስርዓቶች) ያፋጥነዋል። ይህ እንደ ክብደት መቀነስ፣ የእጅ መንቀጥቀጥ እና ፈጣን ወይም መደበኛ ያልሆነ የልብ ምት የመሳሰሉ ብዙ ምልክቶችን ሊያስከትል ይችላል።

ካልታከመ፣ ሃይፐርታይሮይዲዝም በልብዎ፣ በአጥንትዎ፣ በጡንቻዎችዎ፣ በወር አበባ ዑደትዎ እና በመራባት አቅምዎ ላይ ከባድ ችግሮች ሊያስከትል ይችላል። 

የሃይፐርታይሮይዲዝም መንስኤዎች 

ሃይፐርታይሮይዲዝም በተለያዩ ሁኔታዎች ሊከሰት ይችላል።

  • የግሬቭስ በሽታ (Graves’ disease): ይህ የሃይፐርታይሮይዲዝም ዋናው መንስኤ ነው። በግሬቭስ በሽታ፣ የሰውነትዎ መከላከያ ስርዓት (immune system) የታይሮይድ እጢዎን በማጥቃት ከመጠን በላይ ሆርሞን እንዲለቀቅ ያደርጋል። ይህ ሁኔታ ብዙውን ጊዜ በወጣት እና በመካከለኛ ዕድሜ ላይ ባሉ ሴቶች ላይ ይገኛል፣ እንዲሁም በቤተሰብ ውስጥ የመከሰት አዝማሚያ አለው።
  • ከመጠን ያለፈ አዮዲን (excess iodine): የታይሮይድ ሆርሞን ለመመረት አዮዲን ስለሚያስፈልግ፣ ከመጠን በላይ አዮዲን መውሰድ (በምግብ ወይም በመድኃኒት) የሆርሞን ምርትን ሊጨምር ይችላል። አዮዲን በአንዳንድ መድኃኒቶች እና የባህር አሳዎች ውስጥ ይገኛል።
  • ታይሮዳይተስ (Thyroiditis): ይህ የታይሮይድ እጢ ብግነት ነው። ብግነቱ መጀመሪያ ላይ የታይሮይድ ሆርሞን ከመጠን በላይ እንዲለቀቅ ያደርጋል። ከጊዜ በኋላ ግን ሆርሞኖቹ መመርት እንዲቀንሱ አድርጎ የታይሮኢድ ሆርሞን እጥረት ያስከስታል። ይህ በሽታ ብዙውን ጊዜ ጊዜያዊ ምልክቶችን ያስከትላል።
  • የታይሮይድ እጢ እባጮች (Toxic thyroid nodules /Toxic adenoma): እነዚህ በታይሮይድ እጢዎ ላይ የሚፈጠሩ አንድ ወይም ከዚያ በላይ የሆኑ ሌሎች ዕጢዎች ናቸው። አብዛኛውን ጊዜ ጤናማ (ካንሰር ያልሆኑ) ናቸው። ነገር ግን እነዚህ እባጮች ራሳቸውን ችለው ከመጠን በላይ የታይሮይድ ሆርሞን ማምረት ሊጀምሩ ይችላሉ። የታይሮይድ እጢ እባጮች በእድሜ የገፉ ሰዎች ላይ በብዛት ይከሰታሉ።
  • የእንቁላል ወይም የወንድ የዘር ፍሬ እጢዎች (Tumors of the ovaries or testes): እነዚህ ያልተለመዱ ዕጢዎች የታይሮይድ ሆርሞኖችን የሚያመርቱ ህዋሳትን ሊይዙ ይችላሉ።
  • ከመጠን ያለፈ የታይሮይድ መድኃኒት: ይህ የሚከሰተው የታይሮይድ ሆርሞን እጥረት ያለባቸው ሰዎች የታይሮይድ ሆርሞን መድኃኒት ከመጠን በላይ ሲወስዱ ነው።

የሃይፐርታይሮይዲዝም ምልክቶች

የሃይፐርታይሮይዲዝም ምልክቶች አንዳንዶቹ በግልጽ የሚታዩ ሊሆኑ ቢችሉም፣ ሌሎች ደግሞ ስውር ሊሆኑ እና መጀመሪያ ላይ ለመለየት አስቸጋሪ ሊሆኑ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ ሃይፐርታይሮይዲዝም እንደ ጭንቀት (anxiety) ያሉ ለሎች የጤና እክሎች ጋር ሊመሳሰል ይችላል። ይህ ደግሞ ለመመርመር አስቸጋሪ ያደርገዋል። ከእነዚህ ምልክቶች አንዳንዶቹን ብቻ ሊያጋጥምዎ ወይም ብዙዎቹን በአንድ ጊዜ ሊያጋጥምዎ ይችላል። ሁሉም ሰው የተለያየ ስለሆነ ሁሉንም ምልክቶች ላያዩ ይችላሉ፣ እንዲሁም ምልክቶቹ በድንገት ሊጀምሩ ወይም ከጊዜ ወደ ጊዜ ቀስ በቀስ ሊመጡ ይችላሉ።

የሃይፐርታይሮይዲዝም ዋና ዋና ምልክቶች የሚከተሉት ናቸው

  • የምግብ ፍላጎት መጨመር ቢኖርም ክብደት መቀነስ 
  • ፈጣን ወይም መደበኛ ያልሆነ የልብ ምት መኖር
  • ድካም መሰማት፣ ነገር ግን ለመተኛት መቸገር
  • የልብ ትርታ መሰማት ወይም መደበኛ ባልሆነ መንገድ እየመታ ያለ መስሎ መሰማት (heart palpitations) 
  • የደም ግፊት መጨመር
  • የእጅ ወይም የምላስ መንቀጥቀጥ (tremors) እና የጡንቻ ድክመት
  • ጭንቀት፣ መረበሽ እና/ወይም መበሳጨት መሰማት
  • የስሜት መለዋወጥ (Mood swings)
  • የእንቅልፍ ችግሮች መኖር 
  • ከመጠን ያለፈ ንቃት (hyperactivity) እና ዝም ብሎ መቀመጥ መቸገር 
  • በቀላሉ ሙቀት መሰማት፣ ሙቀትን አለመቻል እና ላብ መጨመር
  • የወር አበባ ዑደት ለውጦች
  • ተቅማጥ ወይም በተደጋጋሚ መጸዳዳት።
  • ሞቅ ያለና እርጥብ ቆዳ መኖር
  • እንቅርት (ጎይትር/goiter) ወይም የታይሮይድ እጢ ማበጥ። ይህም በሁለት በኩል ወይም በአንድ በኩል ብቻ ሊሆን ይችላል። 
  • የአይን ወደውጪ መውጣት (Exophthalmos) እና/ወይም ከዓይኖች ጀርባ ህመም 
  • የሚሰባበር ፀጉር እና የፀጉር መርገፍ ሊያስከትል ይችላል።

ከ60 ዓመት በላይ የሆናቸው አዋቂዎች ከወጣቶች የተለዩ ምልክቶች ሊኖራቸው ይችላል። ለምሳሌ፣ የምግብ ፍላጎታቸውን ሊያጡ ወይም ከሌሎች ሰዎች ሊርቁ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ ይህ እንደ ድባቴ ወይም የመርሳት ችግር (dementia) ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በተጨማሪም አረጋውያን ታካሚዎች በብዛት የመተንፈስ ችግር፣ መደበኛ ያልሆነ የልብ ምት እና ያልተገለጸ ክብደት መቀነስ ይታይባቸዋል። 

ለሃይፐርታይሮይዲዝም አጋላጭ ሁኔታዎች

ለሃይፐርታይሮይዲዝም የመጋለጥ ዕድልዎን የሚጨምሩ ምክንያቶች የሚከተሉትን ያካትታሉ፡-

  • ፆታ: ሴቶች ከወንዶች ይልቅ በሃይፐርታይሮይዲዝም የመያዝ ዕድላቸው ከፍተኛ ነው። ባለሙያዎች ይህ ከሆርሞኖች ጋር የተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ያምናሉ።
  • እርግዝና: በእርግዝና ወቅት በአንዳንድ ሰዎች ላይ ሃይፐርታይሮይዲዝም ሊፈጠር ይችላል፣ ይህም ለእናትም ሆነ ለፅንሱ ውስብስብ ችግሮች ሊያስከትል ይችላል። እርግዝና በተለይም ከወሊድ በኋላ ለሚከሰተው ታይሮዳይተስ (postpartum thyroiditis) ተጋላጭ ያደርጋል።
  • ዕድሜ: በተለይም ከ60 ዓመት በኋላ በእድሜ በገፉ አዋቂዎች ለሃይፐርታይሮይዲዝም የመጋለጥ ዕድላቸው ከፍተኛ ነው።
  • ዘረመል (Genetics): በቤተሰብ ውስጥ የሃይፐርታይሮይዲዝም ታሪክ መኖር ሁኔታውን የመፍጠር ዕድልን ይጨምራል።
  • ከመጠን በላይ አዮዲን ካገኙ፡ ከፍተኛ መጠን ያላቸውን አዮዲን የያዙ ምግቦችን መመገብ ወይም አዮዲን የያዙ መድኃኒቶችን መጠቀም ለሃይፐርታይሮይዲዝም የመጋለጥ እድልን ይጨምራል። 
  • ሌላ የጤና እክሎች መኖር: እንደ ዓይነት 1 የስኳር በሽታ፣ የአድሬናል እጥረት (primary adrenal insufficiency)፣ በቪታሚን B12 እጥረት ምክንያት የሚከሰት የደም ማነስ (pernicious anemia) ወይም ሌሎች ሥር የሰደዱ በሽታዎች ያለባቸው ሰዎች ለበሽታው የመጋለጥ ዕድላቸው ከፍተኛ ነው።
  • ማጨስ: ይህ በተለይ ለግሬቭስ በሽታ የመጋለጥ እድልን ይጨምራል።

ሃይፐርታይሮይዲዝም ካልታከመ ምን ያስከትላል?

ያልታከመ ሃይፐርታይሮይዲዝም ለሚከተሉት ችግሮች መጨመር አስተዋጽኦ ያደርጋል፡-

  • የታይሮይድ ስቶርም (Thyroid storm): የታይሮይድ ስቶርም ባልታከመ ሃይፐርታይሮይዲዝም ምክንያት የሚከሰት ያልተለመደ የጤና ሁኔታ ነው። ከመጠን በላይ በሆኑ የታይሮይድ ሆርሞኖች ምክንያት ሰውነትዎ ወደ ከፍተኛ ንቃት (overdrive) ውስጥ ይገባል። የታይሮይድ ስቶርም ለሕይወት አስጊ የሆኑ ምልክቶች ስብስብ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ ፈጣን የልብ ምት፣ ከፍተኛ የደም ግፊት፣ ትኩሳት፣ ማቅለሽለሽ፣ ማስታወክ፣ ተቅማጥ ወይም ድርቀት፣ መደናገር ይገኙበታል። በአጠቃላይ ይህ ድንገተኛ የሃይፐርታይሮይዲዝም ምልክቶች መባባስ ሲሆን በኢንፌክሽን፣ እርግዝና፣ መድኃኒትዎን በትክክል አለመውሰድ እና የታይሮይድ እጢ ላይ በሚደርስ ጉዳት( ለምሳሌ ጉሮሮ ላይ መመታት) ሊነሳ ይችላል። ይህ ሁኔታ አስቸኳይ የህክምና እርዳታ ያስፈልገዋል።
  • የእርግዝና ችግሮች: ይህ ቀደም ሲል የታይሮይድ ችግር ያለባቸውን ሰዎች እና በእርግዝና ወቅት ሃይፐርታይሮይዲዝም የሚያጋጥማቸውን ሰዎች ያጠቃልላል። ከፍተኛ የታይሮይድ ሆርሞን መጠን ነፍሰ ጡር የሆኑትን ሰዎችም ሆነ ፅንሱን ሊጎዳ ይችላል። በእርግዝና ወቅት ከመጠን በላይ የሆነ የታይሮይድ ሆርሞን ካለ እና ሁኔታው በቁጥጥር ስር ካልሆነ የፅንስ መጨንገፍ (miscarriage)፣ ያለጊዜው መውለድ (premature birth)፣ ልጁ ሲወለድ ዝቅተኛ ክብደት ይዞ መወለድ እና በእርግዝና ላይ የሚከሰት ደም ግፊት(pre-eclampsia) ሊያስከትል ይችላል። በእርግዝና ወቅት የታይሮይድ ሆርሞን መጠንን መመርመር እነዚህ ችግሮች እንዳይፈጠሩ ይረዳል። ሐኪምዎ በመጠኑ ላይ በመመርኮዝ ለህክምና አስፈላጊነት ይወስናል። በተጨማሪም አንዳንድ የሃይፐርታይሮይዲዝም መድሃኒቶች ጽንሱ ላይ ችህግር ሊያመጡ ይችላሉ። ስለዚህም ካርቢማዞል (carbimazole) የሚወስዱ ከሆነ ወይም ባለፉት 6 ወራት ውስጥ የራዲዮአክቲቭ አዮዲን ሕክምና ካደረጉ የእርግዝና መከላከያ መጠቀም በጣም አስፈላጊ ነው። በነዚህ ህክምናዎች ውስጥ ሆነው እርግዝና ከተፈጠረ ወዲያውኑ ለሐኪምዎ ያናግሩ። ካርቢማዞል የሚወስዱ ከሆነ ልጅዎን በማይጎዳ ሕክምና፣ ለምሳሌ ፕሮፒልቲዮራሲል (propylthiouracil) ወደ ሚባል መድኃኒት እንዲቀይሩ ሊመክር ይችላል።
  • በቀላሉ የሚሰባበር አጥንት/ ኦስቲዮፖሮሲስ (Osteoporosis): ሃይፐርታይሮይዲዝም አጥንቶችዎ እንዲዳከሙና እንዲሳሱ ሊያደርግ ይችላል፣ ይህ ሁኔታ ኦስቲዮፖሮሲስ (Osteoporosis) ይባላል። በሕክምና ወቅት እና ከህክምና በኋላ የቫይታሚን ዲ (vitamin D) እና ካልሲየም (calcium) የሚጨምሩ መድሃኒቶችን መውሰድ የአጥንትን ጤና ለማሻሻል ይረዳል። ከሃይፐርታይሮይዲዝም ሕክምና በተጨማሪ በቂ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ ወይም የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ማድረግ ኦስቲዮፖሮሲስን ለመከላከል ይረዳል።
  • ካንሰር: አንዳንድ የካንሰር ዓይነቶች ከሃይፐርታይሮይዲዝም ጋር ሊታዩ ይችላሉ። የ2018 ጥናት ሃይፐርታይሮይድ በሽተኞች ላይ የታይሮይድ ካንሰር የበለጠ የከፋ እንደነበር እና ጤናማ ታይሮይድ ካላቸው (euthyroid) ታካሚዎች ይልቅ የከፋ ውጤት እንደነበረው ዘግቧል።
  • የልብ ችግሮች፡ የሃይፐርታይሮይዲዝ በጣም አሳሳቢ ከሆኑት የጎንያሽ ጉዳቶች መካከል ልብ ላይ የሚፈጥረው ተጽኖ አንዱ ነው። ከነዚህም መካከል የልብ ድካም (Congestive heart failure) እና የልብ ምት መዛባት (Atrial fibrillation) ይጠቀሱበታል። እነዚህም ልብ ለሰውነት ክፍሎች በቂ ደም ማሰራጨት የማይችልበት ሁኔታን ይፈጥራሉ፣ በተጨማሪም ለስትሮክ (stroke) ተጋላጭነትን ይጨምራሉ።
  • የማየት ችግሮች (Vision problems)፡ አንዳንድ የሃይፐርታይሮይዲዝም ያለባቸው ሰዎች የታይሮይድ ዓይን በሽታ (thyroid eye disease) ወይም የግሬቭስ ኦፍታልሞፓቲ (Graves' ophthalmopathy) የሚባል ችግር ያጋጥማቸዋል። ይህ በተለይ ሲያጨሱ በብዛት ይታያል። የግሬቭስ በሽታ ባለባቸው ከ4 ሰዎች መካከል 1 ያህሉን ይጎዳሉ።  ይህ መታወክ በአይን ዙሪያ ያሉትን ጡንቻዎችና ሌሎች ሕብረ ሕዋሳትን ይነካል። እነዚህ ምልክቶች አብዛኛውን ጊዜ የታይሮይድ በሽታው ሲታከም ይሻሻላሉ። ነገር ግን አንዳንድ ሰዎች በዓይኖቻቸው ላይ ያለው ችግር ሊቀጥል ይችላል። የዓይን ችግሮች ካለብዎት ለህክምና ወደ የዓይን ስፔሻሊስት (ophthalmologist) ሊላኩ ይችላሉ። እንደ የዓይን ጠብታዎች፣ ስቴሮይድ መድኃኒቶች ወይም ምናልባትም ቀዶ ጥገና ሊታዘዝልዎት ይችላል። 

    የታይሮይድ ዓይን በሽታ ምልክቶች የሚከተሉትን ያካትታሉ፡-

    • ዓይን ወደውጪ መውጣት(Bulging eyes)
    • በዓይን ውስጥ የአሸዋ ስሜት መኖር(Gritty sensation)
    • የዓይን መድረቅ
    • በዓይን ውስጥ ግፊት ወይም ህመም
    • ያበጡ ወይም ወደ ኋላ የተመለሱ የዐይን ሽፋኖች (Puffy or retracted eyelids)
    • ቀይ ወይም ያበጡ ዓይኖች።
    • ብርሃን ማየት አለመቻል(Light sensitivity)
    • ድርብ እይታ (Double vision)
    • የማየት ችሎታን ማጣት
  • የቆዳ ችግሮች፡ አልፎ አልፎ፣ የግሬቭስ በሽታ ያለባቸው ሰዎች የቆዳ ችግሮች (Graves' dermopathy) ያጋጥማቸዋል። ይህ ቆዳው ቀለም እንዲለወጥ፣ እንዲደርቅ  እና እንዲጠነክር ያደርጋል። ብዙውን ጊዜ በቁርጭምጭሚት እና በእግር ላይ ያገጥማል።
  • የታይሮይድ ሆርሞን ማነስ (Underactive thyroid)፡ ለሃይፐርታይሮይድዝም የሚሰጠው የራዲዮአክቲቭ አዮዲን ሕክምና (radioactive iodine treatment) ብዙውን ጊዜ የሆርሞን መጠን በጣም እንዲቀንስ ያደርጋል። ይህ የታይሮይድ ሆርሞን ማነስ/ ሃይፖታይሮይድዝም (hypothyroidism) በመባል ይታወቃል። ምልክቶቹ የሚከተሉትን ሊያካትቱ ይችላሉ፡- ድካም፣ ክብደት መጨመር፣ የሆድ ድርቀት፣ የመንፈስ ጭንቀት፣ እናቅዝቃዜ ስሜታዊነት። ይህ ሁኔታ አንዳንዴ ለጊዜው ብቻ የሚቆይ ነው፣ ነገር ግን ብዙውን ጊዜ ለረጅም ጊዜ የታይሮይድ ሆርሞን መድኃኒት መውሰድ ያስፈልጋል።

ሃይፐርታይሮይዲዝም እንዴት ይመረመራል? 

ሃይፐርታይሮይዲዝም እንዳለብዎ ለመገምገም ዶክተርዎ የእርስዎን የግል እና የቤተሰብ የህክምና ታሪክ ይሰበስባል እንዲሁም የአካል ምርመራ ያደርጋል። ዶክተሮች ብዙውን ጊዜ ሃይፐርታይሮይዲዝምን በምልክቶች እና በላብራቶሪ ምርመራዎች ላይ በመመርኮዝ ይለያሉ። በደም ምርመራ ውጤቶች ላይ በመመስረት፣ ሌሎች ምርመራዎችም ሊያስፈልጉ ይችላሉ።

እነዚህ ምርመራዎች የሚከተሉትን ያካትታሉ፡-

  • ታይሮክሲን (T4)፣ ትራይአዮዶታይሮኒን (T3) እና የታይሮይድ ሆርሞን እንዲመነጭ የሚያደርግ ሆርሞን (TSH) መጠን ምርመራ: እነዚህ ምርመራዎች በደምዎ ውስጥ ያለውን የታይሮይድ ሆርሞን መጠን ይለካሉ። ከፍተኛ የታይሮክሲን(T4) ደረጃ እና ዝቅተኛ የታይሮይድ ሆርሞን እንዲመነጭ የሚያደርግ ሆርሞን (TSH) ደረጃ ሃይፐርታይሮይዲዝም ባለባቸው ሰዎች የሚታይ ነው። የታይሮይድ ሆርሞን እንዲመነጭ የሚያደርግ ሆርሞን (TSH) የሚመረተው ፒቱታሪ በሚባል እጢ ሲሆን የታይሮይድ እጢ ሆርሞን እንዲያመነጭ ያነሳሳል። በሃይፐርታይሮይዲዝም ጊዜ፣ የታይሮይድ ሆርሞኖች መጠን ከፍተኛ ስለሆነ የፒቱታሪ ግራንት TSH ምርትን ይቀንሳል (ስለዚህ የ TSH ደረጃዎች ብዙውን ጊዜ ይሆናሉ)።

    ባዮቲን የተባለውን ቪታሚን ቢ ሰፕልመንት ከወሰዱ የታይሮይድ የደም ምርመራዎች የተሳሳተ ውጤት ሊሰጡ ይችላሉ። ትክክለኛ የደም ምርመራ ለማግኘት፣ ዶክተርዎ ከምርመራው ከ 3 እስከ 5 ቀናት በፊት ባዮቲን መውሰድ እንዲያቆሙ ሊጠይቅዎት ይችላል።

  • የታይሮይድ ስካን(Thyroid scan): ይህ ምርመራ የታይሮይድ እጢዎ አዮዲን የሚወስድበትን መንገድ ያሳያል እና የሃይፐርታይሮይዲዝምን መንስኤ ለመለየት ይረዳል። ለዚህ ምርመራ ትንሽ መጠን ያለው ራዲዮአክቲቭ የሆነ አዮዲን (radioiodine) ይወስዳሉ፣ ይህም በታይሮይድ እጢዎ ውስጥ ምን ያህል እንደተከማቸ እና የት እንደተከማቸ ለማየት ይጠቅናል። 

    የታይሮይድ እጢዎ ከፍተኛ መጠን ያለው ራዲዮአዮዲን ከወሰደ፣ ይህ ማለት የታይሮይድ እጢዎ ከመጠን በላይ የታይሮይድ ሆርሞን እያመረተ ነው ማለት ነው። በጣም ሊከሰት የሚችለው መንስኤ የግሬቭስ በሽታ ወይም ከመጠን በላይ አመንጪ የሆኑ የታይሮይድ እጢዎች ናቸው። የታይሮይድ እጢዎ ዝቅተኛ መጠን ያለው ራዲዮአዮዲን ከወሰደ፣ ይህ ማለት በታይሮይድ እጢ ውስጥ የተከማቹ ሆርሞኖች ወደ ደም ውስጥ እየፈሰሱ ነው ማለት ነው። በዚህ ሁኔታ፣ የታይሮኢድ ብግነት/ ታይሮዳይተስ የመሆን እድሉ ከፍተኛ ነው።

  • የታይሮይድ አልትራሳውንድ: ይህ ምስል የታይሮይድ እጢዎን ቅርፅ እና በውስጡ ያሉ እባጮችን (nodules) ለመመልከት ይረዳል። በዚህ ምርመራ የጨረር ተጋላጭነት ስለሌለ፣ ለነፍሰ ጡር ወይም ለሚያጠቡ ሰዎች እንዲሁም ራዲዮአዮዲን መውሰድ ለማይችሉ ሌሎች ሰዎች ሊያገለግል ይችላል።
  • ሲቲ (CT) ወይም ኤምአርአይ (MRI): እነዚህ አልፎ አልፎ ጥቅም ላይ የሚውሉ ሲሆን የታይሮይድ እጢ ወይም የፒቱታሪ እጢ ለውጦችን ለመመልከት ሊረዱ ይችላሉ።
  • የ ፀረ-ታይሮይድ ሆርሞኖች (Thyroid antibodies) መጠን ምርመራ: እነዚህ ምርመራዎች እንደ ግሬቭስ በሽታ ያሉ መንስኤዎችን ለመመርመር ይረዳሉ።
  • ብግነት መኖሩን ለማረጋገት የሚረዱ ምርመራዎች (ESR): በሰውነትዎ ውስጥ ብግነት መኖሩን ለማጣራት ሊደረግ ይችላል። የብግነት ምልክቶች ካሉ፣ የታይሮይድ ሆርሞኖች መጨመር ታይሮዳይተስ(የታይሮይድ ብግነት) ምክንያት ሊሆን ይችላል።

ሃይፐርታይሮይዲዝምን እንዴት ማከም ይቻላል? 

ለሃይፐርታይሮይዲዝም በርካታ ሕክምናዎች አሉ። ለእርስዎ የሚስማማው ዘዴ በእድሜዎ እና በጤንነትዎ ላይ የተመሰረተ ነው። የሃይፐርታይሮይዲዝም መሰረታዊ መንስኤ እና ምን ያህል ከባድ እንደሆነም ልዩነት ይፈጥራል። የሃይፐርታይሮይዲዝም ሕክምና ዓላማው ከመጠን በላይ የሆነውን የታይሮይድ ሆርሞን ምርት መቀነስ ወይም ማቆም ነው። ዋናዎቹ የሕክምና ዘዴዎች የሚከተሉት ናቸው፡-

 1. መድኃኒት (Medication)

  • ፀረ-ታይሮይድ መድኃኒቶች (Anti-thyroid medications):

እነዚህ መድኃኒቶች ታይሮይድ ሆርሞኖችን እንዳያመነጭ ይከላከላሉ። በጣም የተለመዱት ፀረ-ታይሮይድ መድኃኒቶች ቲኦአማይድስ (thioamides) የሚባሉ ሲሆን፣ ሜቲማዞል (methimazole/MMI) እና ፕሮፒልቲዮራሲል (propylthiouracil/PTU) የተባሉትን መድኃኒቶች ያካትታሉ። ምልክቶቹ ብዙውን ጊዜ ከጥቂት ሳምንታት እስከ ወራት ውስጥ መሻሻል ይጀምራሉ። ሕክምናው ብዙውን ጊዜ ከ 12 እስከ 18 ወራት ይቆያል። ከዚያ በኋላ ምልክቶቹ ከጠፉ እና በደም ምርመራዎች ላይ የታይሮይድ ሆርሞን ደረጃዎች ወደ መደበኛ ክልል ከተመለሱ መጠኑ ቀስ በቀስ ሊቀንስ ወይም ሊቆም ይችላል። ነገር ግን አንዳንድ ሰዎች ለብዙ ዓመታት ወይም ምናልባትም ለሕይወት መድኃኒት መውሰድ መቀጠል አለባቸው። አልፎ አልፎ ቢሆንም፣ በሁለቱም ፀረ-ታይሮይድ መድኃኒቶች ከባድ የጉበት ጉዳት ሊከሰት ይችላል። ነገር ግን ፕሮፒልቲዮራሲል ብዙ የጉበት ጉዳቶችን ስላስከተለ፣ ሰዎች ሜቲማዞል መውሰድ በማይችሉበት ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ ይውላል። 

በመጀመሪያዎቹ ሁለት ወራት ውስጥ አንዳንድ ሰዎች ማቅለሽለሽ/የመታመም ስሜት፣ ከፍተኛ ሙቀት፣ ራስ ምታት፣ የመገጣጠሚያዎች ሕመም፣ የሆድ መረበሽ፣ ማሳከክ እና ሽፍታ ሊያጋጥማቸው ይችላል። ብዙም ያልተለመደ ነገር ግን ይበልጥ አሳሳቢ የጎንዮሽ ጉዳት በድንገት የነጭ የደም ሴሎችዎ ቁጥር መቀነስ (agranulocytosis) ሲሆን ይህም ለኢንፌክሽኖች በጣም የተጋለጠ ያደርግዎታል። ከፍተኛ ትኩሳት፣ የጉሮሮ መቁሰል ወይም የማያቋርጥ ሳል የመሳሰሉ ምልክቶች ካጋጠሙ ወዲያውኑ ሐኪምዎን ያነጋግሩ። ካርቢማዞል በእርግዝና ወቅት መውሰድ ፅንሱን ሊጎዳ ስለሚችል ካርቢማዞል እየወሰዱ ከሆነ ውጤታማ የወሊድ መከላከያ መጠቀምዎን ያረጋግጡ።

  • ቤታ ብሎከርስ (Beta blockers)

እነዚህ መድኃኒቶች የታይሮይድ ሆርሞን ደረጃዎችን አይነኩም። ነገር ግን እንደ መንቀጥቀጥ ፣ ፈጣን የልብ ምት እና የልብ ምት መዛባት ያሉ የሃይፐርታይሮይዲዝም ምልክቶችን ሊቀንሱ ይችላሉ። አንዳንድ ጊዜ ዶክተሮች የታይሮይድ ሆርሞኖች ወደ መደበኛ ደረጃ እስኪጠጉ ድረስ ምልክቶችን ለማስታገስ ያዝዛሉ። እነዚህ መድሃኒቶች በአጠቃላይ አስም ላለባቸው ሰዎች አይመከሩም። እንደ ጎንዮሽ ጉዳት ድካም እና የወሲብ ችግሮችን ሊያካትቱ ይችላሉ።

  • ስቴሮይድ (Steroids):

የታይሮይድ ብግነትን (ታይሮዳይተስ) ለማረጋጋት ሊያገለግሉ ይችላሉ።

2. ራዲዮአክቲቭ አዮዲን (Radioactive iodine/RAI)

ራዲዮአክቲቭ አዮዲን ሕክምና የታይሮይድ እጢ ውስጥ ያሉትን ሴሎች ለማጥፋት የሚያገለግል የህክምና ዓይነት ነው፣ ይህም የሚያመነጨውን የሆርሞኖች መጠን ይቀንሳል። የታይሮይድ ሆርሞኖችን በብዛት የሚያመነጩትን ሴሎች ያጠፋል እንጂ ሌሎች የሰውነት ሕብረ ሕዋሳትን አይጎዳም። በተጨማሪም ይህ ህክምና በከፍተኛ መጠን የታይሮይድ ካንሰርን ለማከምም ያገለግላል። ብዙውን ጊዜ በአፍ በሚወሰድ ኪኒን ወይም ፈሳሽ መልክ ይሰጣል። አብዛኛዎቹ ሰዎች አንድ ጊዜ ሕክምና ብቻ ያስፈልጋቸዋል። ሙሉ ውጤቱ እስኪማጣ ድረስ ጥቂት ሳምንታት ወይም ወራት ሊወስድ ስለሚችል፣ ለጥቂት ጊዜ እንደ ካርቢማዞል ወይም ፕሮፒልቲዮራሲል ያሉ መድኃኒቶችን መውሰድ ሊያስፈልግዎ ይችላል።

በራዲዮአክቲቭ አዮዲን ሕክምና ወቅት ጥቅም ላይ የሚውለው የጨረር መጠን በጣም ዝቅተኛ ነው፣ ነገር ግን ከሕክምናው በኋላ ሊወስዷቸው የሚገቡ አንዳንድ ጥንቃቄዎች አሉ፡-

  • ለ3 ሳምንታት ያህል ከህጻናት እና ነፍሰ ጡር ሴቶች ጋር ረጅም የቅርብ ግንኙነትን ያስወግዱ
  • ሴቶች ቢያንስ ለ 6 ወራት እርጉዝ መሆን የለባቸውም
  • ወንዶች ቢያንስ ለ 4 ወራት ልጅ ለመውለድ መሞከር የለባቸውም

ራዲዮአክቲቭ አዮዲን ሕክምና እርጉዝ ወይም ጡት ለሚያጠቡ ሴቶች ተስማሚ አይደለም። በሃይፐርታይሮይዲዝም ምክንያት የዓይን ችግሮች እየተፈጠረ ከሆነም ተስማሚ አይደለም። ለሃይፐርታይሮይዲዝም ራዲዮአዮዲን ሕክምና የሚያገኙ አብዛኛዎቹ ሰዎች ተቃራኒውን ሁኔታ፣ ማለትም ሃይፖታይሮይዲዝም/ የታይሮይድ ሆርሞን እጥረት (hypothyroidism) ያጋጥማቸዋል። በዚህ ምክንያት፣ ከጊዜ በኋላ የታይሮይድ ሆርሞኖችን ለመተካት መድኃኒት መውሰድ ሊያስፈልግዎ ይችላል።

3. ቀዶ ጥገና (Surgery)

የታይሮይድ እጢ ቀዶ ጥገና ታይሮይድክቶሚ (Thyroidectomy) የሚባል ሲሆን በዚህ ቀዶ ጥገና ወቅት የታይሮይድ እጢዎ በሙሉ ወይም በከፊል ይወገዳል። የሃይፐርታይሮይዲዝም ምልክቶች እንዳይመለሱ ስለሚያደርግ ሁሉንም የታይሮይድ እጢ ማስወገድ በአጠቃላይ ይመከራል። ነገር ግን ሃይፐርታይሮይዲዝምን ለማከም ብዙ ጊዜ ጥቅም ላይ አይውልም። እርጉዝ ለሆኑ ሰዎች እንዲሁም ፀረ-ታይሮይድ መድኃኒት መውሰድ ለማይችሉ እና ራዲዮአዮዲን ሕክምናን መውሰድ ለማይፈልጉ ወይም ለማይችሉ ሰዎች ምርጫ ሊሆን ይችላል። 

የቀዶ ጥገና ህክምናው ለሚከተሉት ሁኔታዎች ተመራጭ ነው ፡-

  • በትልቅ እንቅርት ምክንያት የታይሮይድ እጢዎ በጣም ካበጠ
  • ከባድ የዓይን ችግሮች ከተከሰትብዎት 
  • ሌሎች ሕክምናዎችን መውሰድ ካልቻሉ
  • ሌሎች ሕክምናዎችን ከሞከሩ በኋላ ምልክቶችዎ ከተመለሱ

ነገር ግን አንዳንዴ ይህ ህክምና የድምጽ ቱቦ እና ፓራታይሮይድ እጢዎች (በደም ውስጥ ያለውን የካልሲየም መጠን የሚቆጣጠሩ አራት ትናንሽ እጢዎች) መጎዳትን ያካትታሉ። 

የታይሮይድ ቀዶ ጥገና ወይም ራዲዮአዮዲን ሕክምና የሚያደርጉ ሰዎች ሌቮታይሮክሲን (levothyroxine) የሚባል መድኃኒት የዕድሜ ልክ ሕክምና ያስፈልጋቸዋል። ይህ መድኃኒት ለሰውነት የታይሮይድ ሆርሞኖችን ይሰጣል። በቀዶ ጥገና ወቅት የፓራታይሮይድ እጢዎች ከተወገዱ፣ የደም ካልሲየም ጤናማ በሆነ ክልል ውስጥ እንዲቆይ ለማድረግም መድኃኒት ሊያስፈልግ ይችላል።

 

ለሃይፐርታይሮይዲዝም የሚጠቅሙ የአኗኗር ዘይቤ ለውጦች እና የቤት ውስጥ ሕክምናዎች 

ሕክምና ሲጀምሩ፣ የሃይፐርታይሮይዲዝም ምልክቶችዎ ሊሻሻሉ ይችላሉ። ከሕክምናዎ ጋር፣ በአመጋገብዎ ውስጥ ያለውን አዮዲን እንዲቀንሱ ሊጠቅም ይችላል። የአዮዲን ምንጮች: የባህር አሳዎች እና የባህር አረም ዓይነቶች ብዙ አዮዲን ይይዛሉ። የሳል ሽሮፕ (cough syrup) እና ብዙ ቫይታሚኖችም አዮዲን ሊይዙ ይችላሉ።

ለግሬቭስ በሽታ ሕክምናዎች (Graves' disease)

የዓይን ወይም የቆዳ ችግሮችን ለሚያመጣብዎት የግሬቭስ በሽታ፣ የሚከተሉትን እርምጃዎች መውሰድ ምልክቶችን ለማስታገስ ይረዳል።

  • ለዓይን ችግሮች 
    • አያጨሱ: ማጨስ የታይሮይድ የዓይን በሽታ መከሰት ጋር ተያይዟል። በተጨማሪም ሁኔታውን ሊያባብሰው ይችላል እንዲሁም ከሕክምና በኋላ ምልክቶች እንዲመለሱ ሊያደርግ ይችላል።
    • የዓይን ጠብታዎች ይጠቀሙ: ድርቀትን እና መቧጨርን ለማስታገስ ሊረዱ ይችላሉ።
    • በቀዝቃዛ እና ረጠብ ባለ ንጹህ ጨርክ ያቀዝቅዙት (Cool compress)
    • በመኝታ ሰዓት ዓይኖችዎ ሙሉ በሙሉ ካልተዘጉ፣ ኮርኒያ እንዳይደርቅ ለመከላከል በመኝታ ሰዓት የሚቀባ ጄል ሊረዳ ይችላል። አንዳንድ ሰዎች ሲተኙ የዐይን ሽፋኖቻቸውን በቴፕ ይለጥፋሉ።
    • ዓይንዎን ይጠብቁ : ከፀሐይና ከነፋስ ለመከላከል የፀሐይ መነፅር ያድርጉ።
    • ራስዎን ከፍ ያድርጉ: የአልጋዎን የራስጌ ክፍል ከፍ ማድረግ እብጠትን ሊቀንስ እና በዓይንዎ ላይ ያለውን ግፊት ሊያቃልል ይችላል።
  • ለቆዳ ችግሮች (Pretibial Myxedema)
    • ክሬሞችን ይጠቀሙ: በቁርጭምጭሚትና በእግር ላይ ያለውን ቆዳ ለማከም ሃይድሮኮርቲዞን (hydrocortisone) የያዙ ክሬሞች ሊረዱ ይችላሉ።

Comments (0)